1 እንደገናም እግዚአብሔር በእስራኤል ላይ እጅግ ተቆጣ፤ ዳዊትንም በእነርሱ ላይ በማስነሳት፣ “ሂድ እስራኤልንና ይሁዳን ቁጠር” አለው፡፡ 2 ንጉሡ አብሮት ለነበረው ለኢዮአብ፣ “ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ወደ እስራኤል ነገዶች ሁሉ ሂዱ፣ ለጦርነት ብቁ የሆኑትንም ጠቅላላ ብዛት ማወቅ እችል ዘንድ ሕዝቡን ሁሉ ቁጠሩ፡፡” አለው፡፡ 3 ኢዮአብም ለንጉሡ፣ “እግዚአብሔር አምላክህ የሕዝቡ ቁጥር መቶ እጥፍ ያብዛ፣ የጌታዬ የንጉሡ ዓይንም ይህንን ለማየት ያብቃው፡፡ ነገር ግን ጌታዬ ይህንን ለማድረግ ለምን ፈለገ?” 4 ይሁን እንጂ የንጉሡ ቃል የኢዮአብንና የሠራዊት አለቆችን ቃል የሚሽር የመጨረሻ ቃል ነበር፡፡ ስለዚህ የእስራኤልን ሕዝብ ይቆጥሩ ዘንድ ኢዮአብና የሠራዊቱ አለቆች ከንጉሡ ፊት ወጡ፡፡ 5 ዮርዳኖስን ተሻገሩና ከከተማው በስተደቡብ በሸለቆው ዘንድ ባለው በአሮዔር አጠገብ ሠፈሩ፡፡ ከዚያም በጋድ በኩል አድርገው ወደ ኢያዜር ተጓዙ፡፡ 6 ወደ ገለዓድና ወደ ተባሶን አደሰይ፣ ቀጥሎም ወደ ዳንየዓን ከዚያም ዞረው ወደ ሲዶና ሄዱ፡፡ 7 ወደ ጢሮስ ምሽግና ወደ ኤዊያውያንና ወደ ከነዓናውያን ከተሞች ደረሱ፡፡ ከዚያም በይሁዳ ቤርሳቤህ ወዳለችው ወደ ኔጌቭ ወጡ፡፡ 8 በመላው ምድሪቱ ከተዘዋወሩ በኋላ ከዘጠኝ ወር ከሃያ ቀናት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፡፡ 9 ከዚያም ኢዮአብ ለንጉሡ የተዋጊ ወንዶችን ጠቅላላ ቁጥር ዘገባ አቀረበ፡፡ በእስራኤል ሰይፍን መምዘዝ የሚችሉ ስምንት መቶ ሺህ ጀግኖች ሲኖሩ በይሁዳ ደግሞ አምስት መቶ ሺህ ሰዎች ነበሩ፡፡ 10 ሰዎቹን ከቆጠረ በኋላ ዳዊት በልቡ ተጨነቀ፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር፣ “ይህንን በማድረጌ ታላቅ ኃጢአት ሠርቻለሁ፡፡ የሠራሁት እጅግ የስንፍና ሥራ ነውና፣ እግዚአብሔር ሆይ፣ የባሪያህን በደል አስወግድ፡፡” 11 ዳዊት ጠዋት ከመኝታው ሲነሣ፣ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዳዊት ባለ ራእይ ወደ ነቢዩ ጋድ እንዲህ ሲል መጣ፣ 12 “ሂድና ለዳዊት፣ ‘እግዚአብሔር የሚለው ይህንን ነው፣ ሶስት ምርጫ እሰጥሃለሁ፣ አንዱን ምረጥ’” 13 ስለዚህ ጋድ ወደ ዳዊት ሄደና፣ “የሦስት ዓመት ረሃብ ወደ ምድርህ ይምጣን? ወይስ እነርሱ እያሳደዱህ ከጠላቶችህ ለሶስት ወራት ብትሸሽ ይሻልሃል? ወይስ በአገርህ የሶስት ቀን ቸነፈር ይምጣብህ? ለላከኝ ምን መልስ እንደምሰጥ አሁን ወስን” አለው፡፡ 14 ዳዊትም ጋድን፣ “እጅግ ተጨንቄአለሁ፤ ምሕረታዊ አደራረጉ እጅግ ታላቅ ስለሆነ በእግዚአብሔር እጅ እንውደቅ እንጂ በሰው እጅ አንውደቅ” አለው፡፡ 15 ስለዚህ እግዚአብሔር ከጥዋት እስከ ተወሰነ ጊዜ ቸነፈሩን በእስራኤል ላይ ላከ፣ ከዳን እስከ ቤርሳቤህም ሰባ ሺህ ሰዎች ሞቱ፡፡ 16 መልአኩ ኢየሩሳሌምን ለማጥፋት እጁን በዘረጋ ጊዜ፣ እግዚአብሔር ስለደረሰው ጉዳት ተፀፀቶ ሕዝቡን እያጠፋ የነበረውን መልአክ፣ “ይበቃል፣ እጅህን ሰብስብ” አለው፡፡ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ በኢያቡሳዊው በኦርና ዐውድማ አጠገብ ቆሞ ነበር፡፡ 17 ሕዝቡን እየቀሠፈ የነበረውን መልአክ ባየ ጊዜ ዳዊት ለእግዚአብሔር፣ “ኃጢአት ሠርቻለሁ፣ የማይገባም ነገር አድርጌአለሁ፡፡ ነገር ግን እነዚህ በጎች ምን ያደረጉት ነገር አለ? እባክህን የአንተ እጅ እኔንና የአባቴን ቤተሰብ ይቅጣ፡፡” ብሎ ለእግዚአብሔር ተናገረ፡፡ 18 ከዚያ በኋላ ጋድ በዚያን ቀን ወደ ዳዊት መጣና፣ “ውጣና በኢያቡሳዊው በኦርና አውድማ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሥራ” አለው፡፡ 19 ስለዚህ ዳዊት ጋድ እንደ ነገረውና እግዚአብሔር እንዳዘዘው ወጣ፡፡ 20 ኦርና ሲመለከት ንጉሡና አገልጋዮቹ ሲደርሱ አየ፡፡ ስለዚህ ኦርና ወጣ ብሎ በንጉሡ ፊት ለጥ ብሎ እጅ ነሣ፡፡ 21 ከዚያ በኋላም ኦርና፣ “ጌታዬ ንጉሡ ወደ ባሪያው ዘንድ ለምን መጣ?” ዳዊትም መለሰ፣ “ቸነፈሩ ከሕዝቡ ይወገድ ዘንድ ለእግዚአብሔር መሠዊያ የምሠራበትን የአንተን ዐውድማ እገዛ ዘንድ ነው፡፡” 22 ኦርናም ለዳዊት፣ “ጌታዬ ንጉሡ የራስህ አድርገህ ውሰደው፡፡ በፊትህ ደስ ያሰኘህንም አድርግበት፡፡ እነሆ፣ ለሚቃጠል መሥዋዕት በሬዎች፣ ለማገዶም የሚሆን የመውቂያ ዕቃና ቀንበር በዚህ አለ፡፡ 23 ይህንን ሁሉ ንጉሤ ሆይ፣ እኔ ኦርና ለአንተ እሰጣለሁ” አለና ከዚያ በኋላ፣ “እግዚአብሔር አምላክህ ይቀበልህ” አለው፡፡ 24 ንጉሡም ለኦርና፣ “አይሆንም፣ ይህንን በዋጋ መግዛት ይኖርብኛል፡፡ ምንም ነገር ያላወጣሁበትን አንድም ነገር ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት አድርጌ አላቀርብም” አለው፡፡ ስለዚህ ዳዊት ዐውድማውንና በሬዎቹን በሃምሳ የብር ሰቅል ገዛ፡፡ 25 ዳዊት በዚያ ላይ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠራና የሚቃጠል መሥዋዕትና የኅብረት መሥዋዕት አቀረበ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ስለ ምድሪቱ ተለመነው፣ በእስራኤል የነበረውም ቸነፈር ቆመ፡፡