ምዕራፍ 1

1 በይሁዳ ነገሥታት በዖዚያን፥ በኢዮአታም፥ በአካዝና በሕዝቅያስ ዘመን፤በእስራኤልም ንጉሥ በዮአስ ልጅ በኢዮርብዓም ዘመን ወደ ብዔር ልጅ ወደ ሆሴዕ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው። 2 እግዚአብሔር በሆሴዕ አማካይነት መናገር በጀመረ ጊዜ እንዲህ አለው፦« ምድሪቱ እኔን በመተው ታላቅ ምንዝርናን እያደረገች ነውና፥ሂድ፥የምንዝርናዋ ፍሬዎች የሆኑ ልጆች ያሏትን ሴተኛ አዳሪዋን ሚስትህ አድርገህ ውሰድ።» 3 ስለዚህም ሆሴዕ ሄዶ የዴቤላይምን ሴት ልጅ ጎሜርን አገባ፤እርስዋም ጸነሰች፥ ወንድ ልጅም ወለደችለት። 4 እግዚአብሔርም አለው፦ «ከጥቂት ጊዜ በኋላ በኢይዝራኤል ስለነበረው ደም ማፍሰስ የኢዩን ቤት እቀጣለሁና፥ የቤተ እስራኤልንም መንግሥት እንዲያከትም አደርጋለ ሁና ስሙን ኢይዝራኤል ብለህ ጥራው። 5 ይህም በኢይዝራኤል ሸለቆ ውስጥ የእስራኤልን ቀስት በምሰብርበት ቀን ይፈጸማል።» 6 ጎሜር እንደገና ጸነሰች፥ ሴት ልጅም ወለደች። በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር ሆሴዕን እንዲህ አለው፦ «ቅንጣት ታህል ይቅር እላቸው ዘንድ ከእንግዲህ ወዲያ የእስራኤልን ቤት አልምርምና ስሟን ሎሩሃማ ብለህ ጥራት። 7 ነገር ግን የይሁዳን ቤት እምራለሁ፥ እኔም እግዚአብሔር አምላካችው በራሴ አድናቸዋለሁ እንጂ በቀስት፥ በሰይፍ፥ በጦርነት፥ በፈረሶች ወይም በፈረሰኞች አላድናቸውም።» 8 ጎሜር፥ ሎሩሃማን ጡት ካስጣለቻት በኋላ ጸነሰች፥ሌላ ወንድ ልጅም ወለደች። 9 በዚያን ጊዜ እግዚአብሔር እንዲህ አለው፦« ሕዝቤ አይደላችሁምና፥ እኔም አምላካችሁ አይደለሁምና ስሙን ሎዓሚ ብለህ ጥራው ።» 10 ነገር ግን የእስራኤል ቤት ቁጥር ሊለካ ወይም ሊቆጠር እንደማይችል የባሕር አሸዋ ይሆናል። «ሕዝቤ አይደላችሁም» በተባሉበት ቦታ፥«የሕያው አምላክ ሕዝብ ናችሁ» ይባላሉ። 11 የይሁዳ ሕዝብና የእስራኤል ሕዝብ በአንድነት ይሰበሰባሉ። የኢይዝራኤል ቀን ታላቅ ይሆናልና፥ ለራሳቸው አንድ መሪ ይሾማሉ፥ ከምድሪቱም ይውጣሉ።